ፈልግ

የኬንያ የመጀመሪያ ክፍለ ጦር የጸጥታ ኃይል በሄይቲ ከተሰማራ በኋላ ወንበዴዎቹ በመጠኑም ቢሆን አፈግፍገዋል የኬንያ የመጀመሪያ ክፍለ ጦር የጸጥታ ኃይል በሄይቲ ከተሰማራ በኋላ ወንበዴዎቹ በመጠኑም ቢሆን አፈግፍገዋል   (ANSA)

የተባበሩት መንግሥታት የፖሊስ ተልዕኮ በሄይቲ የተወሰነ ተስፋ ማምጣቱ ተገለጸ

በቅርቡ የሽግግር መንግሥት መቋቋሙን እና በኬንያ የሚመራው ዓለም አቀፍ ቡድን ማሰማራቱን ተከትሎ በሄይቲ ስላለው ወቅታዊ የሕግ እና የሥርዓት ሁኔታን እንዲሁም ተስፋዎችን በማስመልከት የራዲዮ ቴሌ ሶሌይል ዳይሬክተር አባ ክላውዲ ዱክለርቪል ከቫቲካን የዜና አገልግሎት ጋር ቃለ ምልልስ አድርገዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

እንደ ጎርጎሮሳውያኑ 2024 የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት በሄይቲ ከ2022 ጀምሮ ከተመዘገቡት ሁሉ የበለጠ ሁከቶች የነበሩባቸው ሲሆኑ፥ በዚህ ዓመት ብቻ ከ2,000 በላይ ሰዎች ከወሮበሎች ጋር በተገናኙ ጥቃቶች ሲገደሉ፥ አምስት ሚሊዮን ሕዝብ ማለትም ከሕዝቡ ግማሽ ያህሉ በምግብ እጦት ስጋት ውስጥ የሚገኙ መሆናቸው ታውቋል።

ከሦስት ዓመት በፊት ፕሬዚደንት ጆቬኔል ሞይስ ከተገደሉ በኋላ እጅግ ድሃዋ የአሜሪካ አህጉር ወራሪ ቡድን አብዛኛውን ዋና ከተማዋን ፖርት-አው ፕሪስን እና ሌሎች ግዛቶቿን በመቆጣጠሩ አገሪቱ ትርምስ አስጥ መግባቷ ይታወሳል። በዚህ ዓመት መጋቢት ወር ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኤሪኤል ሄንሪ ስልጣን ከለቀቁ በኋላ ሁኔታው የተረጋጋ ሆኗል።

እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ሰኔ 12/2024 አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋሪ ኮንይል የሽግግር መንግሥት የማቋቋም እና ከየካቲት 2026 በፊት ምርጫን የማዘጋጀት ሃላፊነት ተሰጥቷቸው ነበር። በዚህ የመጀመሪያው እርምጃ ከሁለት ሳምንታት በኋላ የኬንያ የፖሊስ ሃይሎችን በማቋቋም ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረው የጸጥታ ኃይል ስምሪት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሚደገፈው የብዝሃ-ሀገር የደህንነት ተልዕኮ እንደሆነ ይታወቃል።

ሄይቲ አሁንም በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ትገኛለች
ምንም እንኳን ሄይቲ በዋና ዜናዎች ውስጥ ባትሆንም በደሴቲቱ ያለው አጠቃላይ ሁኔታ አሁንም አሳሳቢ ቢሆንም የተባበሩት መንግሥታት የሰላም አስከባሪ ተልዕኮ አንዳንድ መሻሻሎችን መፍጥሩን በፖርት ኦ ፕሪንስ የሬዲዮ ቴሌ ሶሌይል ዳይሬክተር አባ ክላውዲ ዱክለርቪል ለቫቲካን የዜና አገልግሎት አረጋግጠዋል።

የሄይቲው ካኅን አባ ክላውዲ በማከል እንደገለጹት ባለፈው ሰኔ 18/2016 ዓ. ም. 400 የኬንያ የመጀመሪያ ክፍለ ጦር የጸጥታ ኃይል ከተሰማራ በኋላ ወንበዴዎቹ በመጠኑ ቢያፈገፍጉም አሁንም ብዙ ሰዎች መኖሪያቸውን ጥለው በመሸሽ መንገድ ላይ እንደቀሩ ተናግረዋል።

ወንበዴዎቹ የመዲናዋን ዋና ዋና መንገዶችን በመቆጣጠራቸው ከአንዱ የከተማው ክፍል ወደ ሌላው መዘዋወሩ አስቸጋሪ እንደሆነ እና በቀድሞዋ ፖርት-አው-ፕሪንስ ከተማ ምንም የቀረ ነገር እንደሌ ለአባ ክላውዲ ገልጸው፥ የወንበዴዎቹ ዓላማ ሁከት በመፍጠር እንደ አደንዛዥ እጽ ወይም የአካል ክፍሎችን ለማዘዋወር እና ሕገወጥ ተግባሮቻቸውን ማከናወን እንዲችሉ መሆኑን አብራርተዋል። አባ ክላውዲ ወንጀለኞቹ ከባድ የጦር መሣሪያዎችን ከየት እንደሚያገኙ ተጠይቀው ሲመልሱ፥ ከውጪ በሕገ-ወጥ መንገድ እንደሚገቡ አረጋግጠዋል።

ቀጣይነት ያለው የደህንነት ዋስትና ማጣት
የሄይቲው ካኅን አባ ክላውዲ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኮኒል የወሮበሎች ቡድን መሣሪያቸውን እንዲያስቀምጡ ያቀረቡት ጥሪ ተቀባይነት ይኖረዋል ተብሎ አይታሰብም ብለው፥ በዚህ ቀጣይነት ባለው የደህንነት እጦት ውስጥ የሄይቲ ዜጎች እራሳቸውን ለመከላከል ሲሉ እጃቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ እንዳይደሉ እና “ወንበዴዎች በሕዝቡ ላይ ርህራሄ የሌላቸው ለምን ዓላማ ነው?” ብለው እንደሚጠይቁ አባ ክላውዲ አብራርተዋል።

የሕዝቡ ጥያቄ አንድ እና አንድ እርሱም በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ወንበዴዎች ከሕዝቡ ጋር በማዋሄድ ወደ ማኅበራዊ ሕይወት እንዲመለሱ ማድረግ ቢሆንም፥ ትጥቃቸውን ለመፍታታቸው ምን ዋስትና ይኖረናል? የሚል እንደሆነ አባ ክላውዲ አክለዋል።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የመጀመሪያ ጦር ወደ ሥራ መግባቱን ተከትሎ ከቅርብ ቀናት ወዲህ በአንዳንድ አካባቢዎች ብጥብጥ እያገረሸ መምጣቱን እና ባንዳዎች እራሳቸውን ከፖሊስ ኃይሎች ጥቃት ለመከላከል ሕዝቡን ጋሻ ለማድረግ እንደሚሞክሩ አባ ክላውዲ ለቫቲካን የዜና አገልግሎት ተናግረዋል።

የተባበሩት መንግሥታት የፖሊስ ሃይሎች የተስፋ ጭላንጭል ፈጥረዋል
ሆኖም ጥቂት ተስፋ ሰጪ ምልክቶች አሉ ያሉት አባ ክላውዲ፥ በአገሪቱ የፖሊስ ኃይል ቁጥር መጨመሩ ለሕዝቡ ትንሽ ተስፋ መስጠት እንደጀመረ እና በዓመቱ መጨረሻ ነገሮች እንደሚሻሻሉ ተስፋ የሚያደርጉባቸው ምክንያቶች መኖራቸውን አባ ክላውዲ ተናግረዋል።

“የሄይቲ ሕዝብ ውጊያን የሚያውቅ እና በሕይወት ዘመኑ ሁሉ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ያጋጠመው ሕዝብ እንደሆነ አባ ክላውዲ ገልጸው፥ በጣም አስቸጋሪ እና የተወሳሰቡ ሁኔታዎች ቢያጋጥማቸውም ነገር ግን ዘወትር በሁለት እግራቸው ተመልሰው እንደሚቆሙ እና ይህንን ችግር ለማለፍ ተስፋ እንደሚያደርጉ አስረድተዋል።

ቤተ ክርስቲያን ከሄይቲ ሕዝብ ጎን መቆሟን ቀጥላለች
በሁከት እና በብጥብጥ መካከል ብዙ ዋጋ የከፈለችው ቤተ ክርስቲያን መከራ ውስጥ ከሚገኝ የሄይቲ ሕዝብ ጎን መቆሟን እና የወንጌልን ተስፋ ማምጣቷን እንደቀጠለች፥ በወንበዴዎች በተያዙ በጣም አስቸጋሪ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ ካህናት ቁምስናቸው ውስጥ እንደሚቆዩ እና ምእመናኖቻቸውን ጥለው የትም እንደማይሄዱ አባ ክላውዲ ተናግረዋል።

 

24 July 2024, 16:16